የመስቃን ብዙሃን መገናኛ አውታረ መረብ
Aug 26, 20181 min
ሌት ከዋክብቱ እንደ ፀደይ
አጥለቅልቆን በቀይ አደይ
ሰማዩ ሥጋጃ አጥልቆ
ተሽለምልሞ አንጸባርቆ
ፈክቶ አሸብርቆ ደምቆ
በአዝመራ በአጥቢያ ዐፀድ ሰፍኖ
የዓደይ አዝርዕት ተከሽኖ
በዕንቁጣጣሽ ሰብል ታጥኖ
ኢዮሃ አበባዬ ሆኖ፥
ጨረቃዋ ከቆባዋ፥ ከሽልምልሚት እምቡጧ
ጧ ብላ ከሰንኮፈንዋ፥ ተንዠርግጎ የእንኮይ ቡጧ፥
ድንግል ጽጌ-ረዳ ፈልቃ
ፍልቅልቂት ድምቡል ቦቃ …
ተንሠራፍታ የአበባ ጮርቃ፥
ታድያን ብሌኑ የጠጠረ
ባሕረ-ሃሳቡ የከረረ
የውበት ዓይኑ የታወረ
ልበ-ሕሊናው የሰለለ
አይ፥ አበባ አይደለም አለ፤
አይ፥ እሳት አይደለም አለ፤
ያልታደለ። …
ሰማይ ጨለማ ነው እንጂ፥ እሳት አደል ብሎ ካደ
እቶን ባይኑ እየነደደ።
ከዋክብቱ እንደ ችቦ
በነበልባል ወርቀ ዘቦ
ከፅንፍ ፅንፍ አውለብልቦ
ደመራው እየተመመ
እየፋመ እየጋመ
ደመና እንደንዳድ ሲነድ
መንጸባርቅ ሰደድ ሲወርድ፥
በራሪ ኮከብ ተኩሶ
በአድማሳት እሳት ለኩሶ…
ይኸ እንደኔና እንዳንቺው፥ የውበት ዓይኑ የሰለለ
ሰማይ ጨለማ ነው እንጂ፥ እሳት እኮ አይደለም አለ፥
ያልታደለ። …
… ይቅር ብቻ አንናገርም፥
እኔና አንቺ አንወያይም፤
ለውይይት አልታደልንም
እንዲያው ዝም፥ እንዲያው ዝም … ዝም።
አበባ አንሆን ወይ እሳት
ተጠምደን በምኞት ቅጣት
ሰመመን ባጫረው መዓት
ዕድሜ አችንን እንዳማጥናት፤ …
እሳት አንሆን ወይ አበባ
በሕቅ እንቅ ስንባባ
ባከነች ልጅነታችን፥ እየቃተትን ስናነባ
ሳንፈጠር በሞትንባት
ሳናብብ በረገፍንባት
ሳንጠና ባረጀንባት
አበባ ወይንም እሳት፥ መሆኑን ብቻ አጣንባት።
*************************************************
1966 ዓ.ም.
ብርሀንና ሠላም ማተሚያ ቤት