የመስቃን ብዙሃን መገናኛ አውታረ መረብ
የሼህ ሁሴን ጅብሪል ግጥሞች (ክፍል - 14)

105. ቋንቋቸው ተብታባ ዲናቸው እስላም ነው
አገራቸው ቆላ ልብሳቸው ግልድም ነው
ጦራቸው ክፉ ነው አፈር የሚያስቅም
እኒህ ለሐበሻ መርዝ ናቸው ሹ(ስ)ም?
ከኒህ ጋር መጣላት የለውም ጥቅም::
106. በአሥመራ ወያኔ ከመጣ ችግር
መጀመሪያ አሥመራ ትሆናለች ቀብር
አክሱም ትጠፋለች በአንድ ቀን ጀንበር
ግሼን ላሊበላ ትሆናለች ቀብር
ሁሉም ይሸፍታል ሴት እናኳን ሳይቀር::
107. ስንት እጃኢብ ያያል በዱኒያ የቆየ?
እኛ ባንደርስበት የልጅ ልጅ ጉድ አየ
ጥበብ እንዳይለምድ አሻቅቦ እያየ
የነጮችን ሥራ ብልግናን ገበየ
(አባቷም ዝም አለ ፈርጇን እያየ)::
108. የሳዳቶች ቀለብ ቀንበጥ ሳትረክስ
አላፊው ሳይቅማት ሳትበሰብስ
ትንባሆ ሳይቅማት ተሸጣ ሳትረክስ
ተው አታበላሻት ወንድሜ እየቃምክ አልቅስ
አላህ እንዲያለብስህ ሸማና ቀሚስ::
109. ይሰማኝ እንደሆን ፉቅራን ልምከረው
ለሴት ጫት መቃሙን መትፋቱን ይተው
መብራት አጥፉ እያለ ሰው እንዳያየው
እኔም ዝም አልልም ዲኑን ሲያረክሰው
እንኳን አላህ ጠልቶት ደስ አይልም ለሰው::
110. ብዙ ጉድ አየሁኝ መጅሊስ ተጠርቼ
ቱፍታ ልትመታ ጅስሟን ገልጣ አይቼ
ጸጉሯንና ጡቷን ሲይዟት አይቼ
እራቅ ብዬ ቃምኩኝ እንዳልነካት በእጄ
ሰው ነገረኛ ነው ሐሜቱን ፈርቼ::
111. ጠጅ ጠጣ ይለኛል ሲሩን ሳያውቀው
እኔ ለጠጣሁት ምን ቅናት ያዘው
አላህ ሲይስተው እንጅ ለሰው ብዬ አልተው
ንገሩት ቃልቻን ኋላ እንዳያመው
እንደ መምሬ ጉርሙ ሳላበላሸው::
112. አምስት ወቅት ሶላት ስገድ ብንለው
መርቅኛለሁ አለኝ እዩት ይህን ሰው
ጫቱን ዋጀብ አርጎ ዲኑን ሊያጠፋው
ጫቱን እየበላ ቢሰግድ ምነው?
እኔም ዝም አልልም ዲኑን ሲያረክሰው::
113. ሶላት ካልሰገደ አብሮኝ እንዳይቅም
ሐድራ ያበላሻል የለውም ጥቅም
አይሰግድም ከመባል ሞት አይሻልም
አላህ አይለቀውም እስከ ዘለዓላም
ነገሬ ካልገባው ይጠይቅ ዓሊም::
114. የመተማን ትተን የሐውሳን እናውጋ
ሦስት ቀን ጨልሞ በአራተኛው ነጋ
ለዕለት ታግሎ ነበር ሐውሳ እንዳይወጋ
ስሙ የታወቀ ትልቅ ባለጸጋ
ሳይያዝ ያመልጣል ሐውሳ ግን ተወጋ::
115. ነገሩ እማይገባ የተወላገደ
በአሥመራ በትግሬ ሄዶ እየነደደ
እንዴት ያለ እሳት ከሸዋ ነደደ
ቢያጠፉት እምቢ አለ እየተዛመደ::
116. አንበሳ እግሩን ታሞ ደም ሲያለቃቅስ
ማማው ምስጥ በልቶት ይሆናል ብስብስ
ወደቅ ወደቅ ይላል ወፉን ሊያጨርስ
የዚያን ቀን አሳማ ይሆናል ንጉሥ
ሺምጦ የሚበላ ሰው የሚያስለቅስ::