top of page
  • Writer's pictureየመስቃን ብዙሃን መገናኛ አውታረ መረብ

እግር እንይ! (ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድኅን)


አርቀን ማስተዋል ማለት፣ የኛን ሥልጣኔ ድልድይ

እግር ማየት ነው ብለዋል፣ እስቲ እንግዲህ እግር እንይ!

ያባቶችህ ያይን ድንበር፣ ከተረከዘ ሎሚ ሳያልፍ

አንተ ግን ጆቢራው-ዘራፍ

ጠረፍ አይወስንህ ጉብል

ጥሎ በዘመንህ ዕድል

ዓይንህ ባት አልፎ እንዲዋልል፤

ቴህ ወዲያ ጀግንነት የለ፣ ተዚህ የከረረ ግዳጅ

ባደባባይ የዱር ገደል፣ ስትናደፍ የእግር አዋጅ

ሌሊቱን በየሌት- ‘ግለብ’፣ ቀኑን ጭምር በጠራራ

ሲነጋ እንደጧት ጆቢራ

በከተማህ ስታቅራራ

በዕድሜህ መንከራተት ሥራ፣

ካንዱ ቢሮ ሌላው ቢሮ፣ አቦል በረካውን ብለህ

ያገሩን ወሬ ተንትነህ

ተጨቃጭቀህ ተለፋልፈህ

አመሳጥረህ አቆላልፈህ፣ የዚያን ጉዳይ ከዚህ ጉዳይ

ዘጋግነህ በቡና ምገህ፣ አምተህ ደክመህ ስትለያይ፣

በዚህ ብቻ ሳታስቀረው፣ ደሞ አዲሱን የአገር ጠባይ

ከልማድ የቡና ሱስ ጋር፣ የዘመኑን ሳትለያይ

እስቲ ደሞ አራዳ ወጥተህ፣ በከተማው አደባባይ

ያንዷን ካንዷ ዳሌና ባት፣ እግሯን ከእግር ጋር አስተያይ!

ደርቶልህ ያገር ልጅ ቅልጥም

ዳሌው ባቷ እስኪፈረጥም

እየናረ እስኪያስገመግም

አንተ አድፍጠህ ከኋላዋ፣ በዓይንህ ሣግ ስታነፈንፍ

ያቺን ልክፍ ያቺን ንድፍ

እያረክ ስታሾልቅ፣ አንዷ ፈርታ አንዷ ስታፈጥ

ተጠግታህ ባቷ ሲያገምጥ

“ዘራፍ” ቀርቶ ቀልብህም “ውይ!”

እያለ ወኔህ እግር ይይ!

“በሠየጠኑትማ ዘንድ

አንዱም የባላንጣ ዘዴ፣ የባዕዳን ሥውር መንገድ

ዘመናጥ ጦር መሣሪያ ነው፣ ታዳጊ አገር ለማንጋደድ

እምነቱን ለማወናበድ

ያንድን ትውልድ የሕልም አቅጣጫ

ወደፊት ሳይሆን ወደታች፣ አመንምኖ ማቀጨጫ!”

ቢልህ ፈጥጦ በግልምጫ

ለኅሊናው ማጋለጫ

ናቀው እርግፍ አርገህ ተወው፣ ቴህ ቢጤው ጋር አትንጫጫ፡፡

ሠልጥነን ንቀን አልፈነው፣ የይሉኝታን መቀመጫ

የኛ ዓይን የእግር ነው እንጂ፣ በቅቶት ኅሊና መግለጫ፡፡

እርቀን ማስተዋል ማለት፣ የኛን ሥልጣኔ ድልድይ

እግር ማየት ነው ብለናል፣ አሜን በቃን እግር እንይ!


(ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድኅን)

‘ለእግረተኞች’ - (፲፱፻፷፫ - ‘ፒያሳ’)

39 views0 comments
bottom of page