128. ዘመን ተበላሽቶ ወደቅ ወደቅ ሲል
ነጭ ከባሕር መጥቶ ይስላሉ ሲል
ተፈሪ የዚያን ቀን ይሆናል ትል
ሜዳ ላይ ይወድቃል ሳያገኝ ጅልል::
129. አላህን ሰደብኩት ማን አለው ጠበቃ
ምን ሥፍራ ኖሮት ነው ለራሱ የሚበቃ
በዱኒያ እንደሆነ ይበልጣል የእኔ ዕቃ
ቃልቻ ይመስክር አላህ ካለው ዕቃ::
137. አውራ በሬ ታርዶ አንበሳ ሲያለቅስ
ሐበሻ የዚያን ቀን ትሆናለች ኩስ
ሽታዋ የሚያስከፋ የምታስነጥስ
የዚያን ዕለት ይወድቃል እስላምና ቄስ
የዚያን ቀን ያስፈራል አገር እንዳይፈርስ::
138. እኛ አፈር በገባን በአንድ መቶ ዓመት
ተፈሪ ዓይኑን ታሞ ይገባል መሬት
ማር የላሰ ሁሉ ይቀምሳል እሬት
የበላውም አይቀር ሽቅብ ሲያስተፉት
ካለው ይገድሉታል ለገዘብ ስስት::
139. ሸዋ እባቡን ሳይዝ ምስጢሩን በዝብዞ
ድርቡሽ አገር ገባ የሰውን ላብ ይዞ
እባብ ልቡ አይገኝ መጣ መርዙን ይዞ
ዓለሙ ላይ ተፋው ያገሩን ጅብ ሰዶ
አብሮ የሚበላ አንጀትን በዝብዞ::
140. ሷሊህና ቃሲም አብደላህና ዙበኗር
በወልቃይት ብቅ አሉ ትግሬ ሲበረበር
ኩታበር ገራዶ ትሆናለች ጠጠር
ጎጃም ትጠፋለች ሳትውል ሳታድር
ብዙ ሰው ይጠፋል ያውም ከባላገር::
141. አሥመራ ተወግቶ ወልቃይት መርዙን ተፋ
ሽሬና መቀሌ ይሆናል የከፋ
እንቅልፍ እንዳይወስድህ እርብ ሳይጠፋ
ይመስላል ላየው ሰው ቂያማ የተደፋ
እርብ ስንቱን ጣለው ጠብቆ ወረፋ::
142. ጋይንት ንፋስ መውጫ ድራና ፎገራ
እርብ ላይ ሞልቶ ሲዘፍን ሲያጎራ
ነጋዴው ይጮሃል መቀሌና አሥመራ
ምን ይበጀው ይሆን ጅልጋና ፎገራ?
ሸዋ ደፈረሰ እህሊን ሳይዘራ::
143. መግዛቱን ይገዛል የዮሐንስ ዘር
ወዲያው ለጥቂት ቀን ይላል ፈንጨርጨር
ተፈሪን ጥላ አርጎ ሲያሳድድ ሲቀብር
ቢያዝ ደግ ነበር አገሩን ሳይቀብር
በቀር ሸዋ አይረጋም አትጠራጠር::
144. ሐበሻ ተፈሪን ይዘው ከቀበሩ
አሥመራ በሞላ ይታጠራል በሩ
መቼም ላስተዋለው ብዙ ነው ነገሩ
እኔ እገሌ አልልም ብዙ ነው ምሥጢሩ
በጫካ አካባቢ መች ቀረ ነገሩ::