top of page
  • Writer's pictureየመስቃን ብዙሃን መገናኛ አውታረ መረብ

የሼህ ሁሴን ጅብሪል ግጥሞች (ክፍል - 17)


145. ሐበሻ ስትደኸይ ስትቀጥን እንደ ድር

አዲስ መንግሥት ወጥቶ ይታደላል ምድር

ኸልቁ የዚያን ጊዜ ይለዋል ደንገርገር

ገንዘቡን ተወርሶ አታክልቱም ሳይቀር

እንኳን የተከለው የበረኻው ሳይቀር::


146. ይኸ ቻይና እሚሉት ዘራቸው ካልጠፋ

ችግር ይፈጠራል ይሆናል የከፋ

ማጥፋት ይሻል ነበር በአገር ሳይስፋፋ

ወልደን ሳንጥለው ልጃችን ሳይጠፋ

ጠብቀው ዘመኑን እስኪታይ በይፋ::


147. ሐበሻ ከገባ የቻይና ቁራሽ

ዲንን ያስፈራዋል እንዳይሆን ብላሽ

የዘመኑ ወጣት በሆኑት ቆስቋሽ

ስንቱን አደረጉት ደህይቶ እንዲሸሽ

እንዳይጣቀሙ ሀብታምና አራሽ::


148. ምን መላ ይገኛል ጦር ቢያከማቹት

አልገዛም ካለ ከወንድም ከሴት

ሸዋ ካልመከረ ይሆናል ወንፊት

እባብ መርዙን ከተፋ ይመጣል ፍጅት

ይህን እየሰማህ እንዳትገባ እሳት::


149. በድርቡሽ ሲገርመኝ የመተማ እልቂት

የማይጨው ሲገርመን የአድዋ ጦርነት

መቀሌን አየሁት አረሁ በልቶት

ሸዋ በገዛ እጁ በጫረው እሳት

ስንቱ ሰው ይነዳል ውቅሮ አዲግራት::


150. እንኳን የአንበሳ ልጅ እባብ ሲዞረው

ጀግና የሚወጣበት አገሩ የት ነው

ሥፍራውን ለይቼ እኔ ሳስታውቀው

ሽሬ ልጅ አንበራ ማይጨው ወያኔው

ምኒልክ ይመስክር ሲዋጋ ያየው::


151. የወልይ ልጅ ወልይ፣ የጀግና ጀግና ነው

እኛ እንኳን ባንቀምሰው በሌላው አየነው

በልተው እየጠጡ ጅስማቸው ቀጭን ነው

ወትሮም ደኅና ጎበዝ አካለ ቀጭን ነው

ተፈሪ የማይወፍር ሐሳብ በዝቶበት ነው::


152. ሸዋ አሥመራን ፈጅተህ አቃጥለህ በእሳት

ማምለጫም አታገኝ ሁሴን ፈረድኩት

ግን አሥመራ ያልቃል በራብ በጥማት::


153. ሐበሻ በሞላ በጦር ከተመራ

ወቅትቃቸው ያበቃል ፉቅራና ደብተራ

ለአገር ባይመቹ የሚሠሩት ሥራ

ምድር እያሳዩ ሲያስጥስ ደንቃራ

ጉዳቸው አያልቅም ቢወራ ቢወራ::


154. አሥመራ በጥጋብ ሲዘል ሲደነፋ

የልቡን ተናግሮ ገንዘቡን ሳያጠፋ

እስላም ከክርስቲያን ከሁሉም አይጠፋ

ሁሉም ሊከፋበት በረሃብ ሊያንቀላፋ

ወቅቱ ዘንበል ሲል ያለቅሳል በይፋ::


155. በርበሬ ቢጋገር እንጀራም አይሆን

አዟሪው ማን ይሆን አፍሳሹ ሊጡን?

አቡኪው ማን ይሆናል የሚሰድ እጁን

ሸዋ ግን አይፈራም ያውቀዋል ግዱን

በልቶ ሰው ያስባል እስኪገን አማን::


156. የከተማ ወንፊት በርበሬ እየነፋ

ንፋስ የመጣ እንደሁ ነፊው ዓይኑ ጠፋ

ዓይኑን እስከሚያሸው ነፊ አጥቶ ተደፋ

ንፋስ እያየ ነው በርበሬ የሚነፋ

ፍሬው ካልወደቀ ገለባ አይነፋ::

53 views0 comments

Recent Posts

See All
bottom of page