top of page
  • Writer's pictureየመስቃን ብዙሃን መገናኛ አውታረ መረብ

የሼህ ሁሴን ጅብሪል ግጥሞች (ክፍል - 18)


157. የአሥመራን ልቅሶ ሸዋ ካልሰማው

እንደ ጥቅምት ማር ይልሰዋል ሰው

የጠገበው ጎበዝ ቁንጣን የነፋው

ይጨፈጭፈዋል ዳግሚያ እንዳይለምደው

ቤቱን እስከሚያገኝ በግድ የቀማው::

158. ከቴዎድሮስ አንስቶ ተፈሪ ድረስ

የመኑ ያበቃል ዘውድና ንጉሥ

ንጉሥ አለ ብለህ አትወሳወስ

በምርጫ ካልሆነ የለም የሚነግሥ

ግን ሰውን አየሁት ብዙ ቀን ሲያለቅስ::

159. እያሱ ተረግሞ ሰክሮ ሲያንቀላፋ

ተፈሪ ይነግሣል ሳይደክም ሳይለፋ

ቀጥሎ ያውጃል እንዲያውቁት በይፋ

ፈረንጅን ድል አርጎ ተይዞ ሳይጠፋ

ዘለዓለም የእሱ ናት እስኪሆን አንጋፋ::

160. ሐበሻ ክፉ ነው ቆርጦ ከተነሣ

ፈረንጅን አረጉት ባንዴየ እንዲነሣ

ጦርነት አስቦ ዳግሚያ እንዳይነሣ

አገር መች ይቻላል ቆርቶ ከተነሣ

ሲያዩት ሞኝ ይመስላል ሲነሣ እንደ አንበሳ::

161. እንደ እንቁላል ገምቶ ሲፈርጥ እንደ አምቧይ

ምን ይበጀው ይሆን ባለዛር ጠንቋይ?

ሳትያዝ አትቀርም ዕዳህን ሳታይ

ምን ጠንቋይ ይባላል መጪውን የማያይ

እኛ ባንደርስበት ምንቅሩ ሊታይ::

162. አሥመራና ትግሬ ስትል ሰገደይ

እባብ ከተፍ ይላል ማምጫው ሳይታይ

ሸዋ የዚያን ጊዜ ይላል ዋይ! ዋይ!

ጀርባውን ምች መታው ወደ ትግሬ ሲያይ::

163. ሲተክሏቸው ጥሩ ሲበቅሉ ጠማማ

ታመጣው ይሆናል ወይንስ ከማማ

አላህ ያሳያችሁ የወሎ ኡለማ

ደረጃው ምንድን ነው? ቃልቻው ሰው ታማ

ግን ኋላ ላያቸው ይሆናሉ አሳማ::

164. እንግዲህ የእኔ ጠጅ ነገር ካመጣሽ

ቃልቻ ይጠጣሽ ይታጠብብሽ

ሌላ ሳትነኪ ሐሲድ እያየሽ

ሰው እስኪስቅበት እስኪሆን ብላሽ

በስተቀር ወላሂ ዳግሚያ ላልቀምስሽ::

165. እንግዲህ ቃልቻ አትጫወትብኝ

አንተ እቤቴ ቀርተህ ምንድን ጎደለብኝ?

ትዕቢትህ በስተቀር ሌላ ምን ቀረብኝ::

166. በላ አላህ ይሁንህ የመንደር ቃልቻ

ይኸው አድርገነሃል የቋንቋ ስልቻ

ከቤት እንዳትወጣ ሁን እንደ ጉልቻ

ሴት ወንዱ ያዋርድህ አታግኝ ፈረጃ

በልተህም አትጥገብ ሁን እንደ ስልቻ::

167. የሐበሻ አውሊያ ያሳያችሁ አላህ

እኔ እገሌ አላልሁም በድፍን ሺሊላህ

መቀመጫ አጣሁኝ በቃልቻ ታማሁ

ከፍርሐል በዟሂር አሉኝ ጠጅ ጠጣህ

ከስንቱ ልጣላ አረ የአላህ ያለህ::

30 views0 comments
bottom of page