top of page
  • Writer's pictureየመስቃን ብዙሃን መገናኛ አውታረ መረብ

"የአረንጓዴው ልማት አርበኛ" (በሻኪር አህመድ)


የአረንጓዴው ልማት አርበኛ አቶ መቻል ታደሰ

በቡታጅራ ከተማ በግል ጥረት ቆሻሻ ማጠራቀሚያ የነበረን ስፍራ ወደ አረንጓዴነት የለወጡ የልማት አርበኛ ናቸው !

በከተማችን በከፍተኛ የቆሻሻ መጣያ ስፍራ ከነበሩ ቦታዎች ግንባር ቀደም ተብሎ የሚጠራ ስፍራ ነበር ። ይህም በተለምዶ ሆሳዕና ሆቴል ጀርባ ይባል ነበር ። አሁን ላይ ግን ሙሉ በሙሉ በአረንጓዴ ተሸፍኖ ማራኪ ስፍራ ሆኗል ። አቶ መቻል ታደሰ ይባላሉ ። የባለቤታቸው ስም አልማዝ ፍቃዱ ሲባሉ ሰባት )7) ልጆችን አፍርተዋል። ወደ አረንጓዴው የልማት ከመግባታቸው በፊት ትምህርታቸውን እንደጨረሱ በቡታጀራ ከተማ መለስተኛ እና 2ተኛ ደረጃ ት/ት ቤት በማእከል ሰራተኝነት የትምህረት መረጃ መሳሪያዎችን በማዘጋጀት፣ የትምህርት ቤት የግድግዳ ስዕሎችን በሚሳልና የቤት ውስጥ መገልገያ በእንጨት ስራ ሞያ በማስተማር ይሰሩ ነበር ። አሁን ግን የቤት እቃዎች እና የቢሮ እቃዎች የእንጨት ስራ ባለሙያነት በግል እየሰሩ ይገኛሉ ። በተጨማሪ ከአቦነ ተ/ሀይማኖት ዋሻ ጋር ተያያዥነት የነበረውን የቡታጅራ ከተማ ማዘጋጃ ቤት የቆሻሻ መጣያ ቦታን ወደ አረንጓዴነት በመለወጥ ድንቅ የሆነ ስራ የሰሩ ትጉህና ምሳሌ የሚሆኑ ግለሰብ ናቸው።

አቶ መቻል የአቦነ ተ/ሀይማኖት ዋሻን ተከትሎ ያለውን በተፈጥሮ ወይም ከጥንት ጀምሮ ገደል የነበረውን ቦታ እንዲሁም የማዘጋጃ ቤት የቆሻሻ መጣያ የነበረን ስፍራ ወደ አረንጓዴነት ለመለወጥ መነሻዬ በዋናነት ከልጅነታቸው ጀምሮ ካላቸው የተፈጥሮ ባህሪያቸው የመነጨ ነው። ባለቤታቸውም እንደሳቸው ተፈጥሮን የመንከባከብ ልምድና ማህርይ አላቸው። በልጅነታቸው የቤተሰባቸው እረኝነት ያገለግሉ ስለነበር ሁሌ ማረፊያቸው ጥላ እንደነበር አቶ መቻል ይናገራሉ ። ሁሌም ተጠልዬ ሳለሁ የተለያዩ የእፅዋት የዱር እንስሳት ሲመሽ ደግሞ የእንስሶች ድምፅ መስማት እጅግ በጣም ደስ ይላቸው እንደነበር ይናገራሉ ። ከዚህም የተነሳ ዛፍ ሲቆረጥ ቁጥቋጦና እፅዋቶች በእሳት ሲቃጠሉ ካዩ እጅግ ያዝኑና ያለቅሱ እንደነበር ያስታውሳሉ ። ለምን ታለቅሳለህ ተብለው በወላጆቻቸው መገረፋቸው ያስታውሳሉ ። ትውልዱን ለማስተማር በመወሰናቸው ወደ ተግባር እንዴት ገባህ ለሚለኝ አካል የራሴ ተፈጥሮ ስለሚያስገድደኝ ነው። እኔ ብዙ ሀብት የለኝም። የሙያ የእንጨት ስራ እውቀት ያለኝ ስላለኝ በተፈጥሮ ገደል የሆነው አካባቢ በአቅራቢያው የቤት ውስጥ የመገልገያ እቃዎች ስራ የግለሰብ ቤትን በመከራየት እሰራ የነበር ሲሆን እሪንዛፍ ወንዝ ተከትሎ በተፈጥሮ ገደል ላይ የበቀሉት ትልልቅ ዛፎች ሲቆርጡ እና እፅዋቶች ሲመነጠሩ በአካባቢው የነበሩ የዱር እንስሳት እና አዕዋፋት ሲሰደዱና ሲጠፉ አይቼ እጅግ አዝኜ ባለቤቴን አማክሬ አካባቢውን ለማልማት ማዘጋጃ ቤቱን በ1993 ዓ.ም ሲጠየቁ ስጡ የሚል መመሪያ የለን በሚል መለሱኝ ይላሉ ። እንደገና ከባለቤቴ ተማክረን የደኑ መውደም የሚያስከትለው ችግር ስዕል ስዬ እኔና ባለቤቴ ጥቁር የሀዘን ልብስ ለብሰን አደጋውን የሚገልፀው ስዕል ይዘን ማዘጋጃ ቤት ሄድን ። ለሚመለከተው የወቅቱ ሀላፊ ለአቶ ሚፍታ እና ለአቶ አማረ አቀረብን ። ሀላፊውን ሳያመሰግኑ አላለፉም ። ጥያቄያቸውን ተቀብለው ወዲያው እንዲሰጣቸው ግፊት ተደረገና ተፈቀደላቸው ።

አቶ መቻል ከግብርና የችግኝ ተክል ጠይቀው እና ተፈቅዶላቸው 15,000 ሺ ችግኞችን ተክለው አፅድቀዋል ። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ በተከታታይ 5000 እና ሌላ ተጨማሪ 5000 ችግኞችን የተከሉ ሲሆን በጠቅላላው 25,000 ሺ ችግኞች ተክለዋል ። እንዲሁም እየጠፉ የነበሩ ለመድሀኒትነት የሚያገለግሉ አገር በቀል የእጸዋት ዝርያዎችን ከ300 በላይ ተክለዋል ። አቶ መቻል በገደላማው ቦታው የነበሩ እጸዋቶች ተመንጥረውና ጠፍተው በነበረበት ወቅት ከአካባቢው ሸሽተው የነበሩ የዱር እንሰሳቶችና አዕዋፎች የገደላማው አካባቢ መልሶ በደን በመሸፈኑ ምክንያት ወደ ቀድሞ ቦታቸው የተመለሱ ሲሆን ከተመለሱት የዱር እንስሳት መካከል ጦጣ 200፣ ሽኮኮ 10 ፣ ጃርት 20 ፣ ሚዳቋ 3 በጠቅላላ ድምር 233 ሲሆን የዱር አራዊት ደግሞ ቀበሮ 6 ፣ ጅብ 20 ፣ አገፍ 3 ፣ ነብር መሰል አውሬ 15 ድምር 44 ሲሆን አዕዋፋት ከትንሽ እስከ ትልቅ ከ200 እስከ 400 ይገኙበታል ብለዋል።

አቶ መቻል የተለያዩ ግለሰቦች እና ድርጅቶች የገንዘብ ድጋፍ እንዳደረጉላቸው የገለጹ ሲሆን ይህንኑ ለተባበራቸው የቡታጅራ ከተማ ማዘጋጃ ቤት እኔና ባለቤቴ እጅግ አድርገን ነው የምናመሰግነው ብለዋል ። ለረጅም ጊዜ እስከ መስሪያ ቦታ በመምጣት ምንም የገቢ ምንጭ ሳይኖረን መቸገራችንን ተገንዝቦ ጊዜ፣ ጉልበት እና ገንዘብ ተጠቅመን ባለማነው ስፍራ ቤት ሰርተን የገቢ ምንጭ እንዲኖረን በማሰብ 40 የቤት ክዳን ቆርቆሮ እና ሁለት(2) ፓኬት ሚስማር የግቢ ቧንቧ ውሃ አስገብቶ የቆጣሪውን ክፍያ በመክፈል የተባበረንና በአመት ከአራት ጊዜ በላይ የቀን አበል እስከ 800 ብር በማሰብ የረዳን ለችግኝ መኮትኮቻ 2500 ብር በመስጠት ድጋፍ ያደረገልን ሲሆን በአረንጓዴ ስብሰባ ላይ ተሳታፊ እንድንሆን አድርጓል ብለዋል ። ለማበረታቻ 5,000 ብር መስጠቱን እና ለመብራት ቆጣሪ ክፍያ 5,700 በመክፈል ድጋፍ አድርጎልናል ። እንዲሁም ለቤቱ ስራ የተለያዩ ወዳጆችን ድጋፍና ትብብር በማድረግ ወደ ስፍራው እንድንገባ እድል ፈጥሮልኛል ብለዋል ።

አቶ መቻል ምን ያስደስቶታል ? ለጠየቅናቸው “እንደኔ ከዚህ በላይ ምን ደስታ ይገኛል?” ተፈጥሮን መንከባከብ በምድር ላይ ያሉ ፍጥረታት በሙሉ የህይወት ጉዳይ እኮ ነው ። ምድርን እንድንኖርባት ብርቅዬ የዱር እንስሳት የዱር አራዊት ልዩ ልዩ አዕዋፋት በሙሉ ተመልሰው ከሰው ልጆች ታርቀው ተዛዝነው እና ተሳስበው በደስታ እየፈነጩ አብረው እንዲኖሩበት ለማድረግ ነው የማስበው ብለዋል ።

በመጨረሻም አቶ መቻል ለወደፊት መሟላት ያለባቸው ብለው ያነሱት ሀሳብ ትልቅ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባው የአካባቢው የመንገድ ዳር መብራት ብለዋል ። ያሉበትም ምክንያት በዛ በለማው አካባቢ ጨለማን ተገን ተደርጎ አንድ ሰው አደጋ አድርሰውበት ወደ ጫካው ቢጣል ህብረተሰባችን ይህንን ልማት ሲጠላውና ሲረግመው ይኖራል የሚል የሁልጊዜ ስጋታቸውን ገልፀዋል ። ሌላው በተቻለ መጠን የሚተከሉ ችግኞች ፀድቀው እንዲበቅሉ የዘወትር ሃሳቤ እና ጸሎቴ ነው ብለዋል ። እዚህ ድረስ መጥታችሁ ቃለ ምልልስ ስላረጋችሁልኝ ከልብ አመሰግናለሁ በማለት ለሚድያችን ያለቸውን አድናቆት ጭምር ገልጸዋል ።


“ሁን”

ለተጨነቀ መካሪ

ትልቅ ትንሹን አክባሪ

በሰው ዘንድ ተፈቃሪ

ዕውቀትን አጋሪ

ለስራ ታታሪ

አዲስ ግኝትን ፈጣሪ

ለሌላው ደግሞ አሳቢ

መፅሀፍን አንባቢ

ገንዘብን ቆጣቢ

በቅን ልቦና ሰውን አገልጋይ

ሀብታም ከድሀ የማይለይ

ሁን… ሁሉም በእኩል የሚያይ !

በሻኪር አህመድ

መስቃን ሚድያ ኔትዎርክ ቡታጅራ

60 views0 comments
bottom of page