top of page
  • Writer's pictureየመስቃን ብዙሃን መገናኛ አውታረ መረብ

አሮጌው ገበያ በእሳት ወደመ



ትናንት ማታ እሳት ሀዋሳ ከተማ ውስጥ በገበያ ስፍራዎች ምላሱን ወደ ሰማይ አንጠራርቶ ፣ እንደተራራ ገዝፎ ሲታይ ሁለተኛ ጊዜው ነው ፡፡ አደሱ ገበያ ላይ ያኔ፡፡

አሁን አሮጌው ገበያ ላይ ነው፡፡ ገበያው ውስጥ ከፈተኛ ጉዳት ያጋጠማቸው ቡቲኮች፣ ቀጥሎም እህል ተራው ናቸው ፡፡ ሁለቱም የሰው ልጅ መሰረታዊ ፍላጎቶች ናቸው ፡፡ የቡቲክ ሱቆቹ ሙሉ በሙሉ ወደ አመድነት ተቀይረዋል፡፡ እህል ተራው ተቃጥሎ ፣ በጣም ጥቂት የተረፈው ፣ ተደበላልቆ በአካፋ እየታፈሰ ነው ፡፡ አደጋው የደረሰባቸው ሰዎች እጅግ ያሳዝናሉ፡፡

የኛስ ነገር እንዴት ነው ? እኔ ትናትና ነው ደሞዝ የተቀበልኩት ፡፡ አስቤዛ አልገዛንም፡፡ አሁን ገበያ ስሄድ ምግብ የሚፈልጉ ልጆች የሚያወሩትን ሰምቻለሁ፡፡ አንድ ሳንቡሳ አስር ብር ነው እያሉ ፡፡ የሀዋሳ ገበያ ያልበሰለ ብቻ ሣይሆን የበሰለም ይቀርብበታል ፡፡ ከድንች በዳጣ አስከ ስጋ ወጥ ፡፡

እሳቱን ለማጥፋት የደረሱት የዐደጋ መኪኖች ጉዳት ደርሶባቸዋል ፡፡ የዕሳት አደጋ ማጥፊያው መኪና የፊት መስታወት ተበረቃቅሷል፡፡ የአደጋ ጊዜ አንቡላንስ መኪናም ተገፍታ ወድቃለች፡፡

ከዚህ ተነስተን ምን እንበል? የተደራጀ ሀይል፣ መኪና ገፍቶ የሚጥል ፣ የተደራጀ ሀይል ፣ የእሳት አደጋ መኪና ዕሳቱን እንዳያጠፋ የሚከላከል ስለመኖሩ ምንም ሌላ አስረጅ አያስፈልግም ፡፡ የመንግስት ሰራተኛው አስቤዛ ከሚገዛበት ጊዜ ጋር መገጣጠሙም ሌላ ችግር ነው፡፡ ሀዋሳ ከተማ ውስጥ ይህ ሁሉ ሲሆን የከተማው ፖሊስ በምን ስራ ተጠምዶ ነበር ? መንግስት ከምንላቸው ተቋማት አንዱ እሱም ነው ፡፡

ሀዋሳ ከተማ ውስጥ ነገሮች ‘‘ ጅብ ከሄደ ውሻ ጮኸ’’ ፣ እየሆኑ ተቸግረናል ፡፡ የህግ የበላይነት ይፈፀማል በተባለ ማግስት ህገወጥነት ፡፡ እሳት ሊያጠፋ የመጣ ተሽከርካሪ ላይ ጉዳት ማድረስ ፡፡ ሹፌሩና ረዳቱስ ተርፈው ይሆን?

ሌላም ወደፊት የሚያሰጋኝ ነገር አለ፡፡ ዕድሜያቸው ለህግ ተጠያቂነት የማይበቁ ህፃናትን በገፍ ከተማዋ ውስጥ ተበትነው እና ቤንዚን እየሳቡ፣ በሳቡት ከልክ ያለፈ ቤንዚን ሰክረው ለወንጀል ሲደፋፈሩ እያዩ የሚያልፉት በዋነኛነት የመንገድ መብራት ትራፊኮች አይደሉም? እመኑኝ እነዚህ ህፃናት አንድ ቀን አሁን ከሚፈፅሟቸው ወንጀሎች በላይ የሀዋሳ ከተማ ከፍተኛ ስጋት ናቸው ፡፡

ሀዋሳ ውስጥ አሁንስ የህግ የበላይነት የት ነሽ!!!???......


45 views0 comments
bottom of page