top of page
  • Writer's pictureየመስቃን ብዙሃን መገናኛ አውታረ መረብ

"ቃል-ኪዳን ነበረን" (በወሰን ሰገድገ/ኪዳን)


"ቃል-ኪዳን ነበረን" (በወሰን ሰገድገ/ኪዳን)
"ቃል-ኪዳን ነበረን" (በወሰን ሰገድገ/ኪዳን)

በአንድነት ያቆመ - በአንድ ያስተሳሰረን፣

በፅኑ ተጋምዶ እጅግ የደደረ፣

ዘመናት ያለፈ - ዘመናት የኖረ፣ በላብ የከበረ፣

በደምና በአጥንት የተመሰጠረ፣

በእኔና አንተ መሃል - ቃል-ኪዳን ነበረ።


ከአንተ በፊት ያርገኝ

እኔን ያስቀድመኝ

አንተን ክፉ አይንካህ

እንኳን ሌላው ቀርቶ - ዕንቅፋት አይምታህ

የሚልቃል ነበረን - በእምነት የቀለመ፣

በሀገር ፍቅር ላይ -ፀንቶ የታተመ!


በየተራራው ላይ - “ላብ ደምን ይተካል” እያልን ስንሮጥ፣

ከፍባለ ሞራል - ሶምሶማ ስንረግጥ፣

አምባው ሲንቀጠቀጥ - በሕብረ ድምፃችን፣

በአንድ መቆም ነበር - ደግሞም አብሮ መሞት -የሁሌ ቃላችን!


ኮቾሮ በድንጋይ - ቀጥቅጠን አልመን፣

የቆርቆሮውን ወጥ _ በብረት ባርኔጣ - ገንፈልፈል አድርገን፣

ፍርፍር ቢጤ ሰርተን - እየተጎራረስን፣

ከአንድ ኮዳ ውሃ - ተካፍለን ጠጥተን፣

“ተመስገን” እያልን - በፍቅር ያፀናነው - ቃል-ኪዳን ነበረን!


"ፋሉል ብረት" እሣት - ከላይ ሲዘንብብን፤

አንድ ላይ ልንወድቅ - ወድቀን ልንነሳ - ቃል-ኪዳን ነበረን!

የመድፍና የታንክ ነጎድጓድ ወላፈን፣

ከፀሐይ ንዳድ ልቆ ሲያነደን ሲልፈን

አይዞን ተባብለን፤

ለአንደኛችን መኖር - ከአንዳችን ፊት ቀድመን

ሞትን እንደ ፀጋ - በእምነት ተቀብለን፣

ስለ ሀገር ክብር፣

ሕይወት ልንገብር - በአንድ ዓላማ ፀንተን፣

በደም የከተብነው - ቃል-ኪዳን ነበረን።


ቃልኪዳ ንነበረን - በደም የፀደቀ - በግብር የደመቀ፣

እንኳንስ ያገሩን - የአፍሪካን ወንበዴ - በፅናት ያረቀ፣

ቃል-ኪዳን ነበረን - የማይነቃነቅ፣

ዓለምን ያስቀና - እያደር የሚደምቅ!


በሠላሙ ጊዜ - በአንድ ጋቤጣ እየጠጣን "ስዋ"

ቃልኪዳን ነበረን - አብረን ልንሰዋ!

“አደይ ማርያም” ብለን - አብረን ተገባብዘን፣

በአንድ ትሪ በልተን - በአንድ ዋንጫ ጠጥተን፣

በሐቅ ያደመቅነው _- ቃልኪዳን ነበረን!


የክፉ ቀን ጓድህ - የክፉ ቀን ጓዴ፣

በእምነት ተቆላልፈው - ክንድህና ክንዴ፣

በፍቅር ተጋምደን - በፅናት የቆምን - አልነበርንም እንዴ!?


ምነው በለሊቱ - በድቅድቅ ጨለማ - በድንገት ከዳኸኝ፣

አንተ አለኸኝ ብዬ -የእግዜር ዕንቅልፍ ወስዶኝ፣

አድብተህ እንደአውሬ - እንደእባብ ነደፍከኝ፣

እንዳይሆን አድርገህ ልቤን ሸቀሸቅከኝ!


“አገር አማን ብዬ - ወገን አለኝ ብዬ - ሳሸልብ ጠብቀህ፣

ማተብህን ጥለህ - እምነቴን በጥሰህ፣

ስታዘንብ ጥይት በሰውነቴ ላይ፣

በስተመጨረሻ - ዐይቼህ ነበረ - በቁም ስትሰቃይ፣

ይብላኝ እንጂ ለአንተ - እኔ እንደታመንኩት

ነፍሴ ከመውጣቷ - ከማለፌ በፊት፣

እንደ ተለመደው - ቃል እንደገባሁት፣

“ኢትዮጵያ ወይም ሞት!” - ብዬ ነው የሞትኩት!


ሀገር አልከዳሁም - ወገን አልከዳሁም

ቃል አላፈረስኩም!

ስሄድ እንኳ ከዓለም “ኢትዮጵያ ወይም ሞት” ማለት አልረሳሁም!


“ኢትዮጵያ ወይም ሞት!!


ሕዳር 1 ቀን 2013 ተጻፈ።

31 views0 comments
bottom of page