top of page
  • Writer's pictureየመስቃን ብዙሃን መገናኛ አውታረ መረብ

ወዳጅና ጓደኛዎ ማነው? ስለ ጥርጣሬና አፍራሽ ነገሮች (ክፍል ሁለት)



ክፍል አንድ ላይ ወዳጅና ጓደኛ ምን እንደሆነና እንደት እንደሚገኝ ባጭሩ አቅርቤአለሁ። በክፍል አንድና ሁለት መካከል ያለውን ግንኙነት ለማወቅ መጀመሪያ ክፍል አንድን ማንበብ አለብዎት። እዚህ ሁለተኛው ክፍል ላይ ግን በወዳጅነት መካከል ሊፈጠሩ የሚችሉ ነገሮችን እናያለን። እነሱም መጠራጠርና አፍራሽ ነገር ማሰብ ናቸው።

ጥርጣሬን ማጣራትና ማስወገድ

ጥርጣሬዎች ሁለት አይነት ናቸው። አንደኛው ከውስጣችን የሚመነጭ ጥርጣሬ ነው። ሁለተኛው ከውጭ ወይም በሌላ ሰው ምክንያት የሚመጣ ጥርጣሬ ወይም ወሬ ነው። ከውጭ የሚመጣ ጥርጣሬ ለምሳሌ እከሌ እንዲህ ብሎሃል ሊሆን ይችላል። እከሌኮ ስለ አንተ የሚያስበውና የሚያወራው እንዲህ ነው የሚል ሊሆን ይችላል። ወዳጅነትን ከመሰለ ትልቅ ቁርኝት ላይ ከሌላ ሰው ሰምቶ መወሰን ስህተት ነው። ከሰው በሰሙት ወሬ ምክንያትም ሰበብ መፈለግም አያስፈለግም። እውነት ሊሆንም ስለሚችል ዝም ማለትም አያስፈልግም። ሆኖም ግን መንገዱ የተለያየ ቢሆንም መጠየቅ፣ ማጣራትና ማወቅ አስፈላጊ ይመስለኛል። በደፈናው ረስተንና ንቀን ካልተውነው በስተቀር ዝም ብለን በጥርጣሬ መኖርም አስቸጋሪ ነው። እውነቱን ማወቅ የምንችለው ስናጣራ ብቻ ነው።

ሁለተኛው ደግሞ ከላይ እንደጠቀስኩት ከውጭ ሳይሆን እራሳችን በውስጣችን የምናስበው ጥርጣሬ ነው። ለምሳሌ እከሌን እዚህ ቦታ ስላየሁት እንዲህ ሊሆን ይችላል። እከሌን ከነ እከሌ ጋር ስላየሁት እንደነሱ ሆኗል። የጠረጠርነው ትክክል ሊሆን ይችላል። ውሸትም ሊሆን ይችላል። እውነትና ውሸት ይዞ መኖር ይደብራል። ሆኖም ግን ማወቅና አስፈላጊ ሆኖ ካገኘነው ማጣራቱ ጥሩ ነው። በጥርጣሬ ምክንያት ግን ማጋነንና ሰውን መፈረጅ ስህተት ነው። ጥርጣሬንም መሰረት አድርጉ መወሰን ትክክል አያደርገውም። በተለይ ይህን በተመለከተ ብዙ ኢትዮጵያውያን ይሸወዳሉ። ያሳዝናል። እንደዚህ የሚያስቡ ሰወች ከእውነቱ በፊት የማሰብ፣ የማመዛዘንና የማጣራት አቅማቸውን ከፍ እንደሚያደርጉ ተስፋ አለኝ።

አፍራሽ ነገር ከማሰብ ይልቅ ገንቢ መሆን

በፊትም እንደጠቀስኩት ወዳጅነት የመስጠትና የመቀበል ጉዳይ ነው። ይህ ማለት እያንዳንዱ ሰው በራሱ ወደጅነትን ያፈርሳል ወይም ይገነባል። ይህን ማለት ሰው ባህሪው፣ የሚለውና የሚሰራው ወዳጅነት ላይ ወሳኝ ሚና ይጫወታል። የወዳጅን ሃሳብ ውድቅ ከማድረግና አይሰራም ከማለት ይልቅ፤ እንደት አስበሃል ብሎ መጠየቅ ይሻላል። ይህ ሃሳብህ አይሰራም። በከንቱ ለምን ትለፋለህ። ልክ አይደለህም። እነዚህን የመሳሰሉ አፍራሽ አባባሎች እንኳን ለወዳጅ ቀርቶ ለሌላም ሰው ማለት ያራርቃል እንጅ አያቀራርብም። በምትኩ ግን "ይህ ሃሳብህ አይሰራም" በማለት ፋንታ "ሃሳብህ እንዲሰራ ምን አቅደሃል" ማለት ይሻላል። "በከንቱ ለምን ትለፋለህ" በማለት ፋንታ "ጎበዝ ስለሆንክና ብዙ ስለምትለፋ ውጤትህን መለኪያህ ምንድነው" ብሎ መጠየቅ ይሻላል። "ልክ አይደለህም" በማለት ፋንታ "ምን ለማለት አስበህ ነው" ብሎ መጠየቅ ይሻላል። በህይወታችን ውስጥ ብዙ ነገሮች አባባላቸው ላይ እንጂ ተቀባይነት አላቸው። እርስዎ ግን እንደት ያስቧቸዋል? እንደት ይሏቸዋል? እንደት ያቀርቧቸዋል? ማሰብ፣ ማለትና ማቅረብ ወሳኝነት አለው። እርስዎ ሌላ ሰው ገንቢ ሃሳብ ሲሰጥዎት ደስ እንደሚልዎትና ሞራልዎ ከፍ እንደሚል እርግጠኛ ነኝ። ሌላውም ሰው እንደርስዎ ገንቢ ሃሳብ ማግኘትና መመገብ ይወዳል። ይህን በተጨማሪ ማስታወስ አፍራሽ ከመሆን ይልቅ ገንቢ ለመሆን ይረዳል።


11 views0 comments
bottom of page