top of page
  • Writer's pictureየመስቃን ብዙሃን መገናኛ አውታረ መረብ

ሰው እንደሚበላው ይሆናል- ክፍል አንድ



ሰው እንደሚበላው ይሆናል- ክፍል አንድ

ምግብ ከላይ ለሚታየው ስጋችን እንዳይጎዳ ብቻ ሳይሆን ለውስጥና ለውጭ ጤንነታችንም አስተዋጽኦ አለው፡፡ ስለምግብ ብዙ ነገር ስለሚነገርና ስለሚጻፍ አንዳንድ ጊዜ የትኛውን አይነት ምግብ መብላት እንደሚሻል ለመምረጥ ያስቸግራል፡፡ ስለዚህ የሚስማማንን ምግብና መጠጥ አውቆ መምረጥ መቻልም አስፈላጊ ነው፡፡ ለማንኛውም ባሁኑ ጊዜ ማስታወቂያውና ውድድሩ ስለበዛ አንድ ጊዜ ቀጠንኩኝ ሌላ ጊዜ ደግሞ ወፈርኩኝ እያሉ የሚጨነቁ ጥቂቶች አይደሉም፡፡ እንደ ሁኔታው ሰውነት ሞላ ያለ ወይም ቀጠን ያለ ሊሆን ይችላል፡፡ አንድ ሰው ስለቀጠነ ጤናማ ነው ማለት አይቻልም፡፡ በተመሳሳይም አንድ ሰው ስለወፈረ ችግር አለበት ማለት አይደለም፡፡ ሰው እራሱን መምሰል መቻል አለበት፡፡ ምናልባት የተጋነነ ቅጥነት ወይም ውፍረት ሲሆነ ሃኪምን ማነጋገር የተለመደ ነው፡፡ ዋናው ነገር ግን እያንዳንዱ ሰው የሚስማማውን ምግብና መጠጥ ማወቅ ብቻ ሳይሆን አይነቱንና ልኩንም በተቻለ መጠን ካወቀ ጥቅም እንጂ ጉዳት የለውም፡፡ ለምሳሌ ከለስላሳ፣ ከቢራና አልኮሆል ይልቅ ውኋ በብዛት ማዘውተር የበለጠ ይጠቅማል፡፡ ለምን ቢባል በቀላሉ ነገሩን ውስብስብ ላለማድረግና ሳይንስ ላለማብዛት ለስላሳ፣ ቢራና አልኮሆል በፋብሪካ ስለሚሰሩ ብዙ ጣፋጭና ጭንቅላት የሚያዞር ኮተት አላቸው፤ ውኋ ግን በተፈጥሮ ከሰማይ በዝናብ መልክ ወርዶ ወርዶ ወይም ከመሬት መንጭቶ የተጠራቀመ ነው፡፡

ምግብን በተመለከተ ደግሞ ከመረጥነውና ከወደድነው ምግብ ጋር አትክልትና ፍራፍሬ ማብዛት ጤናማ ነው ምክንያቱም ፍራፍሬና አትክልት ከሞላ ጎደል መሬት ላይ በቅለው ስላደጉ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ደግሞ አስፈላጊውን እንቅስቃሴ ወይም ስፖርት ከተጨመረበት ውጤቱ ያምራል፡፡ የምግብና መጠጥ አይነትና መጠን ከዛም የሚበላበትና የሚጠጣበት ወቅቱ እንጂ የስፖርት ውጤት የምግብና የመጠጥን 1/5ኛ አካባቢ ቢሆን ነው፡፡ ለምሳሌ በቀን ከሶስት እስከ አምስት ጊዜ የሚስማማንን ምግብ አይነት ከልክ ሳያልፍ በመጠኑ መብላት ለጨጓራም ስራ ይስማማዋል፡፡ ስፖርትና ምግብ በተገቢው ከተቀናበሩ ግን ለጤንነት ብቻ ሳይሆን ለመንፈስ እርካታና ለአስተሳሰብ እድገትና መሻሻል፣ ብሩህ ሆኖ ለማሰብም ሆነ ለመጸለይ ጭምር አስተዋጽኦ ያደርጋሉ፡፡ ለዚህ አንዱ ምክንያት የሚሆነው አንድ ሰው በስፖርት፣ በሚበላውና በሚጠጣው ነገር ላይ ስነስርአት ካለው ሌሎች ነገሮችም ላይ ስነስርአት እንዲኖረው በር ሊከፍቱ ስለሚችሉ ነው፡፡

የኢትዮጵያ የምግብ ባህልና ጉርሻ፤

ጉርሻ በራሱ ጥሩና መጥፎ ባይባልም ብዙ ኢትዮጵያውያን ማጉረስና መጉረስ ለምዶብናል፡፡ ማጉረስና መጉረስ ፍቅርና መውደን ማሳያ ቢሆንም ጉርሻ በባህላችን የተጋነነ ነው፡፡ ጉርሻ የምራቅ ንኪኪት ስለሚጨምር በምራቅ ምክንያት የማያስፈልግ ነገር ወደ ሌላ ሰው ማስተላለፊያ አንዱ መሳሪያ ነው፡፡ ማንም ሰው ቢሆን በውስጡ ምን አይነት ኮተት እንዳለው ስለማይታወቅ የግል ወይም የቅርብ ግንኙነት የሌለውን ሰው ማጉረስ አስፈላጊ አይደለም፡፡ ለኛ ለኢትዮጵያውያን ብቻ ሳይሆን ሌሎችም ዜጎች የኛ አይነት የጉርሻ ልምድ ካላቸው ያው ነው፡፡ መጉረስና ማጉረስ ለሚወዱ ሰወች ግን ይህን አባባል ላይወዱት ይችላሉ፡፡ ምግብ የሚበላነት አካባቢ እንተንቆራጠጠ ሌሎች ሲያጎርሱት የሚወድ አለ፡፡ ጉርሻ አልወድም ሲሉትም የሚቀየም አለ፡፡

ሁላችንንም እግዚአብሄርና የሰውነታችን ተፈጥሮዋዊ መከላከያ ሃይል ይጠብቀናል፡፡ ሆኖም ሰወች ስለሆን ለደህንነታችን ተጨማሪ የግል ጥረት ማድረግ አስፈላጊ ነው፡፡ እድሜንም ለማስረዘምና ደስ የሚል ጤናማ ህይወት እንዲኖረን ያግዛል፡፡ በዚሁም አያይዞ ሰው ለግሉም ሆነ ለሌሎች ካሰበና ከተጠነቀቀ የበለጠ ነጻነቱንም ያስከብራል፡፡ ለማኛውም ጉርሻ ወሲባዊ/ኢንቲሜት ጋር የተያያዘ ስለሆነ ከባልና ከሚስት ወይም ከፍቅረኞች ውጭ ሌላ ሰው ማጉረስ የጉርሻን ምንነት ትርጉሙን ይቀንሰዋል፡፡ ባልና ሚስት ወይም ፍቅረኞች ከሆኑ ግን ዞሮ ዞሮ እነዚህ ግለሰቦች በኋላ አብረው ስለሚተኙና የቀረውን ኮተታቸውን ስለሚጨርሱ ምግብም ቢጎራረሱ ያምርባቸዋል፡፡ ጉርሻ ቢበዛ ቢበዛ ከአንድ ቤተሰብ ማለፍ የለበትም፡፡ ለምሳሌ ወላጆች የራሳቸውን ልጆች ማጉረስ ይችላሉ፡፡ በተለይ ወንዱን ወንድ ሲያጎርሰው ደግሞ በጣም ይደብራል፡፡

አብሮ መብላትና መተሳሰብ፤

ሌላው ደግሞ አብሮ መብላት በባህላችን የተለመደ ግሩም ባህል አለን፡፡ ይህን አብሮ በማህበራዊ መብላት ደግሞ በትክክል መጠቀም የምንችል ጥቂቶች ብቻ ልንሆን እንችላለን፡፡ ያው ማህበራዊ ነገሩ እንደተጠበቀ ሆኖ፤ ምግብ ቀርቦ አብሮ በአንድ መሶብ ወይም ትሪ መብላት ማለት የበለጠ እርስ-በርስ እንዲንተሳሰብ የሚያደርግ ቀላል የግላችን ጥረት ያስፈልገዋል፡፡ ያው የኢትዮጵያ ባህል-ምግብ ሲበላ በእጅ ስለሆነ ከሌሎች ጋር በአንድ ላይ ስንበላ የግድ እጆች ወደ እፍ መነከር የለባቸውም፡፡ ከጅ የተረፈ ትራፊ ምግብም እንደገና ወደ መሶቡ መረጨት የለበትም፡፡ ስንቆርስና ማባያ ስናጣብቅም ጠንቀቅ ማለትና ለሌሎች ማስብ አስፈላጊ ነው፡፡ ሰው እንዴት እንደሚበላ የራሱ ምርጫ ቢሆንም ከሌሎች ጋር በአንድ ላይ በምንበላ ጊዜ ግን ለየት ያለ ጥንቃቄና መተሳሰብ ማሳየት ጥሩ ነው ለማለት ነው፡፡

ምንጭ - ታታ


11 views0 comments
bottom of page