top of page
  • Writer's pictureየመስቃን ብዙሃን መገናኛ አውታረ መረብ

የኢትዮጵያዊ እምነትስ እንዴት ነው?



የኢትዮጵያዊ እምነትስ እንዴት ነው?

በየእለቱ ከምናደርጋቸው ብዙወቹ ተግባሮቻችን ውስጥ ከሃይማኖታችን ጋር ብዙ የሚፃረሩ ነገሮችን እናደርጋለን፡፡ ታድያ እርስዎ ስለ እምነትና በራስዎ እምነት ላይ ምን አይነት አመለካከት አለዎት? ስለ ኢትዮጵያውያን እምነትስ? መቼም ሁላችንም በአምላክ ፈጣሪያችን እናምናለን፡፡ ሃይማኖት ማለት ፍቅርና ትክክለኛውን ነገር ማድረግ ማለት ነው፡፡ ጭንቅላት ተሰጥቶናል፡፡ ስለዚህ የተሰጠንን ጭንቅላት በመጠቀም ነገሮችን ካመዛዘን በኋላ ትክክለኛውን ነገር ማድረግ ማለት ነው፡፡ ቅን ማሰብና ማድረግ ደስታን፣ ጤንነትንና እድገትን ያመነጫል! ነገር ግን ብዙዎቻችን ትክክለኛውን ነገር አናደርግም፡፡

ብናደርግማ ኖሮ በመካከላችን ውስጥ ቅራኔ ባልኖረ ነበር፡፡ እራሳችንንም እንችል ነበር፡፡ እንከባበር ነበር፡፡ የእምነትም ሆነ የተግባር ድሃወች ባልሆንን ነበር፡፡ በየእለቱ ከምናደርጋቸው ብዙወቹ ተግባሮቻችን ውስጥ ከሃይማኖታችን ጋር ብዙ የሚፃረሩ ነገሮችን እናደርጋለን፡፡ ለምሳሌ ስንፍና፣ ተንኮል፣ ውሸት፣ ሃሜት፣ ሰውን መንፈግ የመሳሰሉትን፡፡ ይህ ማለት እንግዲህ እምነታችንን በትክክልና በተግባር አንጠቀምበትም ማለት ነው፡፡ ታዲያ ይህ ለምን እንዲህ ሆነ ብለው ሊጠይቁ ይችላሉ፡፡

በራሳችን አስበን ክፉውንና ደጉን መለየት መቻለ አለብን፡፡ ከዚያም ክፉው ነገር ለራሳችንም ሆነ ለሌሎች እንደማይጠቅም እንረዳለን፡፡ ይህንን ካወቅን ክፉ ነገር ከመናገርና ከመስራት እንድንቆጠብ እራሳችንን ለማዘዝ ይረዳናል፡፡ ጥሩ ስነምግባር ተግባራዊ መሆን የሚችለው መጀመሪያ አንድ ሰው በትክክል ሲያምንና አመዛዝኖ ቅን ማድረግ ሲችል ነው፡፡ ቅን ማሰብና ማድረግ ነጻና ገንዘብ የማይከፈልበት የትክክለኛ ዕምነት መሰረት ነው፡፡ ይህ ደግሞ ነጻ ነው! ነገር ግን ከባድና መራራ የሆነውን የራሳችንን ክብር በራሳችን ዝቅ አድርገን ሌሎችን ማክበር ስንችል በቀላሉ እናደርገዋለን፡፡ ይህን ማድረግ የውስጥ ደስታ ይሰጣል፡፡ ተማሪም ይሁን ሠራተኛ፥ የአገር መሪም ይሁን የቤተሰብ አስተዳዳሪ፣ ገበሬም ይሁን ነጋዴ፥ የዚህ አይነቱ ደስታ ባለቤት መሆን ይችላል፡፡ ከዚያም አልፎ በሌሎች ዘንድ ጥሩ ስም ያሰጣል፡፡ በስራ ቦታችን፣ በጎረቤታችን፣ በወገኖቻችን፣ በጓደኞቻችን፣ በዘመዶቻችን፣ ባገራችን ወዘተ ጥሩ ስም ይኖረናል፡፡ ይህንን የውስጥ ደስታ የሚያውቁት ቅን የሚያስቡና የሚያደርጉ ናቸው።

እምነት ምንድነው....

እንግዲህ ሃይማኖት ማለት በእኔ አመለካከት ፍቅር፣ ቅን አስተሳሰብና ቅን ድርጊት ነው፡፡ ታዲያ እኛ ኢትዮጵያውያን ሃይማኖተኞች ነን እያልን እነዚህን ሦስቱን ነገሮች በተግባር እናሳያለን ወይ? አይመስለኝም!!! ቅልስልስ ልስልስ እንላለን እንጂ ብዙወቻችን 'አፉ ቅቤ፥ ልቡ ጩቤ' እንደሚባለው ነን፡፡ ይህ የሚሆነው በማወቅም ይሁን ባለማወቅ ጥሩ ነገር ለመናገርና ለማድረግ ስላልተለማመድን እራሳችንን ማዘዝ ስለማንችልበት ነው፡፡ በህይወታችን፣ በአካባቢያችን እና በአገራችን ላይ የሚከሰቱ ነገሮችንና ጉዳዮችን ጭምር ብዙዎቻችን አመዛዝነን ተገቢውን ውሳኔ መስጠት መቻል አለብን፡፡ ይህ የጥሩ ተግባር እምነት ነው፡፡ ይህ የወገን፣ የአገርና የጥሩ ተግባር ፍቅር ነው፡፡ ሃይማኖትም ነው፡፡

ኢትዮጵያውያን አማኞች ነን፡፡ ይህ በጣም ጥሩ ነው፡፡ ነገር ግን ባለማወቅ ወይም በመወስለት ወይም በተገቢው የሚያስተምረን በማጣት እምነታችን ሙሉ አይደለም፡፡ አሁን ይህንን ስላልኩ ቅር አይበልዎት፡፡ ለምን ይህንን እንዳልኩ እዚሁ ገጽ ላይ አስረዳለሁ፡፡ በተጨማሪ ሙሉ እምነት ማለት ምን ማለት እንደሆነ ማወቅ ከፈለጉ "ጨዋነት" የሚለውን ሁሉንም ክፍል ደጋግመው ቢያነቡ ሊጠቅመዎት ይችላል፡፡ በተጨማሪ ሙሉ እምነት ማለት ምን ማለት እንደሆነ ማወቅ ከፈለጉ "ጨዋነት" የሚለውን ሁሉንም ክፍል ደጋግመው ቢያነቡ ሊጠቅመዎት ይችላል፡፡ የሃይማኖት አስተማሪዎቻችን የሚሰጡት ትምህርት በስራ ክቡርነት ላይ የበለጠ ቢያተኩር ይጠቅማል፡፡ ሰበካው ወይም ትምህርቱ ህዝቡን ለስላሳ፣ ቀለስላሳና ደካማ የሚያደርግ ባይሆን ይመረጣል፡፡ ሰበካው ሁል ጊዜ በእኛና በፈጣሪያችን መካከል ያለውን ግንኙነት ብቻ ሳይሆን ለአገራችን እንድንቆረቆር፣ እርስበርስም እንዲንከባበርና ኢትዮጵያም ማደግ እንደምትችል ቢጨመርበት ይጠቅመናል፡፡

እምነት ስንማር:-

ትምህርቱም ድፍን ያለ እኛን የሚያስጨንቅ መሆን የለበትም፡፡ 'ሰው ካመነ ተራራ ይገፋል' እንደሚባለው ሁሉ እኛ ኢትዮጵያዊያን በስራ ላይም የበለጠ ካተኮርን ማደግ እንችላለን፡፡ ሰው ሥራ ላይ ካተኮረ በሌሎች በማያስፈልጉ አስተሳሰቦችና ድርጊቶች ላይ ለማተኮር ጊዜ የለውም፡፡ ሰበካው ከዕለታዊ ህይወታችን ጋር ተዛምዶ የበለጠ እንድንከባበርና እንድንሰራ የሚገፋፋ ቢሆን ይጠቅማል፡፡ ትምህርቱም በቀላሉ ለመረዳትና ለመፈፀም የሚቻል ቢሆን እድገታችንን ያፋጥነዋል፡፡ ሰርተውና ታግለው ያደጉትንና የተሳካላችውን ግለሰቦች ወይም አገሮች እያነሱ ያለምክንያት መንፈግ ተገቢ አይደለም፡፡ እነሱ እንደዚያ ቢሆኑም እኛ እምነታችን ይበቃናል እያሉ መዶለት በራሱ ሃጢአት ነው፡፡ ስንፍናን ማስተማር ማለትም ነው፡፡ ይህ ይጎዳናል እንጂ አይጠቅመንም፡፡ እከሌ እኮ አለመኛ ነው እያሉ ሰውን መፈረጅም ተገቢ አይደለም፡፡ ሰውን የሚፈርደው አምላክ ፈጣሪያችን እንጂ ሌላ ሰው አይደለም፡፡ ሰው ማንነቱንና ስሙን እንኳን ሳናውቅ 'አምላክን ታውቃለህ?' 'ጌታን ተቀብለሃል?' እያሉ መሳሳት ማፈሪያ መሆን ነው፡፡ ብዙ ጉድ አለን፡፡ አማኞች ነን እያልን እምነታችንን ትክክለኛነቱን የሚያፈርሱ ነገሮች እናደርጋለን፡፡ የሃይማኖት አስተማሪዎቻችን እኛን እንደ ልጆቻቸው ሊያዮን ያስፈልጋል፡፡ ሃላፊነት ተሰምቷቸው ህዝቡ በአግባቡ እራሱን እንዲረዳና እንዲሻሻል ማስተማር መቻል ይጠበቅባቸዋል፡፡

ማንኛውም በመሪነት ደረጃ ያለ ግለሰብ በህዝቡ ዘንድ የተሰሚነት መድረኩ ስላለው ለወገንና ለሃገር፥ ለራሱ ህሊናም ጭምር በጎ ነገር ማድረግና ማስተማር ይጠበቅበታል፡፡ ምሳሌም ሊሆን ያስችለዋል፡፡ 'ሰራ ለነጻነትና ለምግብ' የሚል አዋጅ ቢታወጅ እንዴት ጥሩ ነበር? እኛም በስንፍናችን ምክንያት ስንደኸይ ብቻ ፈጣሪያችንን ማስታወስ ተገቢ አይደለም፡፡ ባገኘንና በሞላልንም ጊዜ ፈጣሪያችንን መርሳት ከንቱነት ነው፡፡ በተንኮላችንም ምክንያት ተሳስተን ወንጀልና ሃጢያት በሰራን ጊዜ ሰይጣን አሳስቶኝ ነው ማለታችንን ማቆም አለብን፡፡ ሰይጣን ማለት እኛና አስተሳሰባችን መሆኑን ማወቅና እራስን መጠየቅ ይጠቅማል፡፡ ስለዚህ ክፉ ነገር ላለማድረግ እራሳችንን ማዘዝ መቻል አለብን፡፡ የጥበብ መጀመሪያም ሆነ መጨረሻ በፈጣሪ ማመንና በጎ ነገርን ለማድረግ እራስን ማዘዝ ነው፡፡ ይህ አባባል ታዲያ የእያንዳንዳችን ህይወት መመሪያ ሊሆን ይገባዋል፡፡ ምግብና ነጻነት በፀሎትና በተአምር ይገኛል ብለን ካመን ድህነትና ነጻነት እጦታችን ይጨምራል እንጂ አምስት ሳንትም አናገኝም፡፡ በተገቢው መንገድ በተቻለን ሁሉ ተግተን መስራት ይኖርብናል፡፡ አባቶቻችንስ 'ማውራት ነው ድህነት፥ መስራት ነው ጌትነት' ብለው የለምን!! ስንፍና ከሃጢዓቶች ውስጥ አንዷ መሆኗንም ማወቁ ይጠቅማል፡፡

በተገቢው መንገድ እራሳችንን፣ ወገናችንንና አገራችንን ለመጥቀም ከሰራን ግን ሃይማኖታችንንም በትክክል መጠቀማችንን ስለሚያመለክት በረከቱንና ብርታቱን ፈጣሪ አምላካችን ያበረክትልናል፡፡ እኔ ፈጣሪ እግዚአብሔር አምላኬን ሳስታውስ የምጠይቀው ''አምላኬ፤ ልቤን ደግ ጭንቅላቴን ደግሞ ብሩህ አድርግልኝ!'' ብዬ እንባ እየተናነቀኝ ይህችን አጭር ጸሎት አደርሳለሁ፡፡ ከዛም ''በተቻለኝ ሁሉ ጎበዝና ጥሩ ሰው ለመሆን እጥራለሁና በረከቱን ስጠኝ'' ብዬ ጸሎቴን እዘጋለሁ፡፡ ይህንንም የምለውና እንባ የሚተናነቀኝ እግዚአብሔርን ስለምወደውና ስለማከብረው ነው፡፡ አሁንም ይህንን ስጽፍ አይኖቼ ጤዛ ሰርተዋል፡፡ ብዙ አገሮችና ዘጎች በተለያዩ ምክንያቶች የተለያዩ ችግሮች አሉአቸው፡፡ ኢትዮጵያም እንደዚሁ፡፡ አምላክ ያመጣውን አምላክ እስከሚመልሰው እያልን ከንፈር መምጠጥና እራሳችን ለፈጠርነው ችግር ወደ ሰማይ እያንጋጠጥን ከአምላክ በፍትሄ መሻት ትክክለኛ አማኞች አለመሆናችንን ግልጽ ያደርገዋል፡፡

እና አምላክ ያመጣውን አምላክ እስከሚመልሰው እያልን ከንፈር መምጠጥና እራሳችን ለፈጠርነው ችግር ወደ ሰማይ እያንጋጠጥን ከአምላክ በፍትሄ መሻት ትክክለኛ አማኞች አለመሆናችንን ግልጽ ያደርገዋል፡፡ በመጀመሪያ ደርጀ ፈጣሪ አምላካችን እኛን ኢትዮጵያውያንን ከሌሎቹ ለይቶ ለመቅጣት ፍላጎት አለው ብየ አላምንም፡፡ በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ ፈጣሪያችን እኛን ብቻ ከሌሎቹ ለይቶ ወይም አዳልቶ እራሳችን ለፈጠርነው ችግር መፍትሄ ይሰጠናል ብዬ አላስብም፡፡ መፍትሄውማ ገና ጥንት ተነግሮናል፤ ተሰጥቶናልም፡፡ መፍትሄው የሚለው ትክክለኛ፣ ጎበዝና ጥሩ ሰው ካልሆንክ የራስህ ስህተት፣ ስፍናና ክፋት ጠልፎ ይይዝሃል ተብሎ ጥንት ተነግሮናል፡፡ ስለዚህ እያንዳንዳችን በእምነታችን ላይ ትክክለኛ፣ ጎበዝና ጥሩ ሰው መሆን ይጠበቅብናል፡፡ ጠቃሚ ለመሆን!!!!

ምንጭ - ታታሪ


26 views0 comments
bottom of page