top of page
  • Writer's pictureየመስቃን ብዙሃን መገናኛ አውታረ መረብ

ነጭ! ነጯን… (በኢዱና አህመድ)


ነጭ! ነጯን… (በኢዱና አህመድ)

“እውነት ተናግሮ የመሸበት ማደር” ይባል የለ?

አንዳንዴ እንደ ወረደ… ነጭ! ነጩን አይነት... ነገርን ማፍረጡ! የግድ እያለ መጥቷል።

ጉራጌ… ጉራጌ… የሚለው ጩኸት እየተበራከተ መጣና ግራ ይግባቸውና... ግራ ያጋቡን ይዘዋል።


ግን... ጉራጌ ምንድን… ማን ነው?


ከስያሜው ብንነሳ “ጉራጌ” የሚለው ስያሜ በአፈ ታሪክ እንደሚነገረው ከሆነ ከሰሜኑ የቀድሞው የኢትዮጵያ ክፍል “ጉራ” ከሚባል ቦታ አሁን ላይ ጉራጌ ዞን ውስጥ የሚገኘው ማህበረሰብ (ወለኔ፣ ቀቤና እና ማረቆን ሳይጨመር) እንደመጣ ይነገራል።

በመስቃንኛ እና በስልጢኛ ቋንቋ ጉራጌ ወይም ጉራ - ጌ የሚለው "ግራ ሐገር" የሚል ትርጓሜ ይሰጠናል። “ጉራ” የሚለው በመስቃንኛ “ግራ” የሚል ትርጓሜ ሲኖረ “ጌ” ደግሞ በስልጢኛ “ሐገር” የሚል ትርጓሜ አለው። ትርጓሜው እንደተገለፀው ይሁን እንጂ ምናልባት ጉራ ከሚባል ሐገር ወይም ቦታ ማህበረሰቡ እንደመጣ ለመግለጽ ሊሆን ይችላል። ነገር ግን ትርጓሜው የመስቃንኛ እና የስልጢኛ ጥምር ቃል እንዴት ሊሆን ቻለ የሚለው ጥያቄን ይጭራል። በእርግጥ ሁለቱም ማህበረሰቦች ኩታ ገጠም በሆነ አካባቢ ስለሚኖሩ የቃላት መወራረስ ሊኖር ይችላል። ቢሆንም የጉራጌ የወል መጠሪያው ትርጉም የሁለት ብሄረሰቦች የቃላት ጥምረት እንዴት ሊመስል ቻለ የሚለው ይበልጡን አነጋጋሪ ነው።


እላይ እንደተገለጸው በመስቃንኛ ቋንቋ የ"ጉራ” አማርኛ ትርጓሜው “ግራ” ሲሆን “ጌ” የሚለው ፊደል በመስቃንኛ ውስን ቃላቶች መጨረሻ ላይ ካስቀመጥነው የተለያየ ትርጉም ይሰጣናል።


ተህኖጌ - የሚለው የመስቃንኛ ቃል “ከእነርሱ ጋር” የሚል የአማርኛ ትርጓሜ ይኖረዋል።

ህኖ በኸኖጌ - የሚለው የመስቃንኛ ቃል “እነርሱ ከሆኑ” የሚል የአማርኛ ትርጓሜ ይኖረዋል።

በኸነጌ - የሚለው የመስቃንኛ ቃል ቃል “ከሆነ” የሚል የአማርኛ ትርጓሜ ይኖረዋል።


እነዚሁ ጉራ ከሚባል ቦታ መጥተዋል የሚባሉት ማህበረሰቦች መስቃን፣ ሶዶ ክስታኔ እና ሰባት ቤት ናቸው። ታዲያ ጉራጌ የሚባሉት ጥምር ማህበረሰቦች በታሪክ ማህበራዊ ግንኙነት ወይም ትስስር እንደሌላቸው የሚታወቅ ሲሆን በተለያየ ጊዜ የጉራጌዎች ማህብራዊ ትስስርን በሚያትት ጽሁፍ ይህንኑ ለመግለጽ ተሞክሯል።


ስያሜያቸውን በተመለከተ፡-

1. ሰባት ቤት

2. ሶዶ ክስታኔ

3. መስቃን


መስቃን እና ሶዶ ክስታኔን በተመለከተ ተከድኖ እንዲቆየን ይሁን። ለዛሬ ግን “ሰባት ቤት” የሚለው ስያሜን በተመለከተ ዳሰሳ እናድርግ። ሰባት ቤት ቃሉ አማርኛ ነው። አሰያየሙ ሰባት የሆኑ ቤተሰቦች ወይም ጎሳዎችን ጥምረትን ለማመላከት ይመስላል። ካልተሳሳትኩኝ በዘጠኙ የጉራጌ ማህበረሰቦች ቋንቋ “ሰባት” የሚለው የአማርኛ ቃል "ሰበት" የሚል የጉራግኛ ትርጓሜ ይኖረዋል። "ቤት" የሚለው ደግሞ ከአማርኛው በተመሳሳይ “ቤት” የሚል ትርጓሜ ይሰጠናል።


ሰባቱ የሰባት ቤት ጉራጌ ቤተሰቦች ወይም ጎሳዎች እንደሚከተሉት ይሆናሉ፡-

1. ቸሃ

2. እዣ

3. ጌቶ

4. ጎማረ

5. እነሞር

6. ምወህር

7. እንደጋኝ


እላይ የተጠቀሱት እና “ሰባት ቤት” በሚል መጠሪያ የተጠቃለሉት ማህበረሰቦች

  • ማን፣ መቼ እና እንዴት የጥምር ስያሜያቸውን ሊያገኙ ቻሉ?

  • የሰባቱ ቤተሰቦች መጠሪያ እንዴትስ አርፍተ ነገር ሊሆን ቻለ?

  • በተጨማሪም መጠሪያቸው እንዴት የአማርኛ አርፍተ ነገር ሊሆን ቻለ?

በኢትዮጵያ የገዚዎችን ታሪክ ለተረዳና እና ላስተዋለ ስያሜው ረጅም እድሜ እንደሌለው የሚያመላክት ፍንጭ ይሰጣል። ከሰባት ቤት ማህበረሰብ በዞን፣ ክልል እና ፌደራል የመንግስት መዋቅር ውስጥ ውስጥ የተሰገሰጉ የሰባት ቤት ተዋለጆች የጉራጌ አንደነት እንቅስቃሴ በማምከን ተጠምደዋል። በተጨማሪም በምስራቅ የጉራጌ ዞን ውስጥ የሚገኙት የመስቃንና የሶዶ ተዋላጅ ሰባት ቤቶቹን በአቅም የሚገዳደሩ አመራሮች ከክልልና ከዞን የመንግሰት መዋቅር በፖለቲካዊ ውሳኔ እንዲነሱና በተለይ የመስቃን ማህበረሰብ በክልል ይሁን በዞን ተወካይ እንዳይኖረው ተደርጓል። የዞን እና የክልሉ ሳይበቃቸው በመስቃን ወረዳዎ ውስጥ በተለያየ የመንግስት መዋቅር ውስጥ የሚሰሩ የመስቃን ተወላጆች በተለመደው ፖለቲካዊ ውሳኔ ከስራ ገበታቸው እንዲባረሩ ተደርገዋል።

እውን እነዚህ የሰባት ቤት ጉራጌ ተወላጅ ተብለው በተለያየ የመንግሰት መዋቅር ውስጥ የሚሰሩ እና በተለያየ የስልጣን እርከን ላይ የሚገኙ አመራሮች ጉራጌዎች ናቸውን? ወይስ በጉራጌ ስም ተልእኮ የተሰጣቸው እና የጉራጌ አንድነት እውን እንዳይሆን ለክፋት የተሰየሙ የሌላ ብሄር ተወላጆች ናቸው?

ሰባቱም ሆነ ዘጠኙ ጉራጌ በሚል የተጠቃለሉት ማህበረሰቦች ውስጣቸውን ሊመረምሩ ይገባል። ለምን ቢባል እራስን እንዲሁም የራስን ማወቅ ደህና ነውና።


መደምደሚያ


ከስያሜው በቀር ማህበራዊ በሆኑ ጉዳዮች ሁሉ ላልተጣመረ እና ላልተዋሃደ በተጨማሪም በክፉ ለሚፈላለግ ማህበረሰብ ጉራጌነቱ ወይም የወል ስሙ ምን ይሰራለታል? ለዚሁም እኮ ነው የአዲሱን የክልል ምስረታን ከመዥገሮቹ ለመላቀቅ ሲባል ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ የምንደግፈው።

ከማእከላዊ መንግሰት በተቀመጠው አቅጣጫ መሰረት የደቡብ ሸዋ ክልልላዊ መንግሰት ምስረታ እውን እየሆነ መጥቷል። የጉራጌ ዞን አመራሮችም ጉዳዩ የግዙፍ ተራራ ያህል ከፊትለፊታቸው ተደንቅሮባቸው እና መፈናፈኛ በማጣታቸው እጅ ወደ ላይ ብለው የክልል ምስረታው ንድፈ ሃሳብ በወረዳ ደረጃ ወርዶ ውይይት ተደረጎበታል። ሁሉም ወረዳዎች በሚባል መልኩ ከተወያዩበት በዃላ የተቀመጠውን አቅጠጣጫ አጽድቀዋል።


እናንት ጉራጌ በሚል ስያሜ የተጨፈለቃችሁ እና ለአመታት በደል የተፈጸመባችሁ ወገኖች እንዲሁም ምሁራን ሆይ… የምትካሱበት ጊዜ በጣም ቅርብ እየሆነ መጥቷል። ደስታውን በወጉ እና በልኩ አጣጥሙት። ነገር ግን ያ… ደስታ እንዳይነጥፍባችሁ ልትጠነቀቁ ይገባል። በተጨማሪም ከታወቅው ጠላት ይልቅ የራስህ የሆነው እና ለምድ የለበስው ሊያጠቃህ ይችላልና እንድትጠነቀቅ ይሁን።


በድጋሚ... ከስያሜው በቀር ማህበራዊ በሆኑ ጉዳዮች ሁሉ ያልተጣመረ እና ያልተዋሃደ በተጨማሪም በክፉ ለሚፈላለግ ማህበረሰብ የጋራ የሆነው ማንነትና መጠሪያ ስሙ ጥንቅር ይበል። በማህበረሰብ መካከል ተቀራራቢ ማንነት እና ቋንቋ ብቻውን አንድነት አይገነባም። በመልካም ምግባርና በመልካም መተሳሰብ ቢሆን እንጂ።

112 views0 comments
bottom of page